በዓለም ለ18ኛ ጊዜ በአገር አቀፍ ደረጃ ደግሞ ለ17ኛ ጊዜ በተከበረው በዓል ላይ የድርጅቱ ሰራተኞች መልካም ስነምግባር ተላብሰው ሙስናን ለመከላከል ለሚደረገው ጥረት ከአመራሩ ጐን መሰለፍ እንደሚጠበቅባቸው ተገለፀ፡፡
“በሥነ ምግባር የታነፀ አመራር ከሙስና ለፀዳች ኢትዮጵያ” በሚል መሪ ቃል ህዳር 29 ቀን 2014 ዓ.ም በተከበረው የዓለም የፀረ ሙስና ቀን ክብረ በዓል ላይ የብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሽታሁን ዋለን ጨምሮ የማኔጅመንት አባላት፤ ቡድን መሪዎች አስተባባሪዎችና ከየስራ ክፍሉ የተውጣጡ ሰራተኞች ተገኝተዋል፡፡

በዕለቱ የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክትና በዓሉን አስመልክቶ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የድርጅቱ ዋና ሥራ እፈፃሚ አቶ ሽታሁን ዋለ “በሥነ ምግባር የታነፀ አመራር ከሙስና ለፀዳች ኢትዮጵያ” የሚለውን የበዓሉን መሪ ቃል አስታውሰው ስነ–ምግባርና መልካም አስተዳደር ማስፈን እንዲሁም ብልሹ አሰራርን ማስወገድ በሀገር ብሎም በድርጅት ደረጃ የሚኖረውን አዎንታዊ ሚና ገልፀዋል፡፡ አያይዘውም እንደዚህ ያሉ በዓላትን ሲከበሩ በዘርፉ ያሉ ችግሮችን በማጤን ለመፍታት በማቀድና ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ የተሰሩ ሥራዎችን በመገምገም ሊሆን እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡
የአመራሩ ሚና እና ቁርጠኝነት ሙስናን ለመከላከል ግንባር ቀደሙን ሚና የሚጫወት መሆኑን ከግንዛቤ ሊወሰድ እንደሚገባ በበዓሉ መክፈቻ ንግግር ያደረጉት የድርጅቱ ስነ–ምግባር ዳይሬክተር አቶ መለሰ በቀለ ገልፀው ያለሰራተኛው ተሳትፎ የአመራሩ ሥነ ምግባር መጠበቅ ብቻ ውጤት ያመጣል ተብሎ እንደማይታሰብና ሠራተኛው መልካም ስነምግባር ተላብሶ ሙስናን ለመከላከል ለሚደረገው ጥረት ከአመራሩ ጐን መሰለፍ እንደሚጠበቅበት በመክፈቻ ንግግራቸው አስገንዝበዋል፡፡
ዳይሬክተሩ አክለውም መንግስት በአሁኑ ጊዜ በሥነ–ምግባር ግንባታ ላይና በሙስና መከላከል ላይ በማተኮር በርካታ ስራዎችን እየሰራ እንደሆነ እና በድርጅቱ የሚከናወኑ ሥራዎች በሙሉ የመልካም ስነምግባር እና የሙስና መከላከል ውጤቶች በመሆናቸው በድርጅታችን ያለው መልካም ውጤት ሁሉ የአመራሩና የሰራተኛው ርብርብ የታከለበት ስለሆነ መልካም ስነ–ምግባር እና ሙስና መከላከል ላይ ትኩረት ሰጥቶ ከተሰራ ውጤቱ ያማረና ከፍተኛ በመሆኑ በቅንጅት የሙስና መከላከል እና የሥነ–ምግባር ግንባታ ሥራ ላይ እናተኩር የሚል መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡

በበዓል አከባበሩ ላይ “የስነምግባርና የሞራል እሴትን በመገንባት እና ሙስናና ብልሹ አሰራርን በመከላከል የኢትዮጵያ አፈፃፀም ከፀረ ሙስና ኮንቬንሽን አኳያ፣” እና “የስነምግባርና የሞራል እሴት ግንባታ ሙስናን ለመከላከል” የሚል ርዕስ ያላቸው ሰነዶች በዳይሬክቶሬቱ ባለሙያዎች የቀረቡ ሲሆን በእለቱ በተካሄደው የጥያቄና መልስ ውድድር አሸናፊዎችን ሽልማት እና ከየስራ ክፍሉ በስነምግባር ለተመረጡ ሰራተኞች የእውቅና ደብዳቤ ተበርክቷል፡፡